አቶ፡ሰይፉ፡ዘለቀ፡በዛ።1920፡ዓ.ም.፡ – ፡2015፡ዓ.ም.። (1928 A.D. – 2023 A.D. )

0
1 0
Read Time:1 Minute, 56 Second
https://youtube.com/live/Z01S92qSm6E?feature=share

በ1920፡ዓ.ም.፥ በዘመነ፡ዮሐንስ፥ ሚያዝያ፡2፡ቀን፥ ማግሰኞ፡ ዕለት፡ሰይፈ፡ሚካኤል፡ዘለቀ፡ተወለዱ።
እናታቸው፡ወይዘሮ፡ደብሪቱ፡ተሰማ፡ዘለ፟ሌ፡እና፡አባታቸው፡አቶ፡ ዘለቀ፡በዛ፟፡በሚኖሩበት፡ደበ፡ጎጆ፡በሚባል፡ቦታ፥ የበኵር፡ልጃቸው፡ አቶ፡ስይፉ፡ዘለቀ፥ ደበ፡ጎጆ፡ይገኝ፡ለነበረው፡ለሚካኤል፡ታቦት፡ ተሰጥተው፡ክርስትና፡ተነሡ።



የመዠመሪያ፡ደረጃ፡ትምህርታቸውን፡ጅማ፡እና፡ዐምቦ፡ ተምረው፡ኹለተኛ፡ደረጃም፡በ”አድቬንቲስት፡ሚስዮን፡ቀበና፟ ፟”፡አቃቂ፡ አጠናቀው፥ በዚያን፡ጊዜ፡በሀገር፡ውስጥ፡”ዩኒቨርስቲ”፡ ስላልተቋቋመ፥ ለከፍተኛ፡ትምህርት፡ወደ፡አሜሪካ፡ኼደው፡ በሕዝብ፡ጤና፡ጥበቃ፡ኹለተኛ፡(“ማስተርዝ”)፡ዲግሪያቸውን፡ እንዳገኙ፥ በመንግሥት፡ጥሪ፥ ላገልግሎት፡ወደ፡አገራቸው፡ ተመለሱ። ጤና፡ጥበቃ፡ሚኒስቴር፡እንዲያገለግሉ፡ሲመደቡ፥ አቶ፡ ሰይፉ፡ዘለቀ፣ አቶ፡ኀይሉ፡ሰብስቤ፡እና፡አቶ፡ዮሐንስ፡ጽጌ፡ በመሥሪያ፡ቤቱ፡ውስጥ፡በ”ዩኒቨርስቲ”፡ደረጃ፡የጤና፡ባለሙያዎች፡ ሦስቱ፡ብቻ፡ነበሩ። ስለዚህም፡የጤና፡ጥበቃ፡ባለሙያዎች፡ ማሠልጠኛ፡ለማቋቋም፡ከባልደረቦቻቸው፡ጋራ፡በመኾን፡የኢትዮጵያ፡ የመዠመሪያ፡የጤና፡ጥበቃ፡ባለሙያዎች፡ማሠልጠኛ፡ክፍልን፡ እንዲሁም፡ሀገራዊ፡የነርስ፡ሙያ፡ምክር፡ቤትንና፡ኮሌጅን፡ በተጨማሪም፡የጐንደር፡ጤና፡ጥበቃ፡ኮሌጅንና፡ማሠልጠኛ፡ ማእከልን፡ቈርቍረው፡መሥርተዋል። ከዚያም፥ ከጤና፡ጥበቃ፡ ባለሙያዎች፡ማሠልጠኛና፡ምደባ፡ክፍል፡ኀላፊነት፡የወባ፡ማጥፊያ፡ ድርጅትን፡በበላይነት፡አንዲመሩ፡ኀላፊነት፡ተሰጣቸው። አቶ፡ሰይፉ፡ ዘለቀ፥ በሙያቸው፡ኢትዮጵያን፡ብቻ፡ሳይኾን፡ሌሎች፡የአፍሪቃ፡ አገሮችንም፡አገልግለዋል። በወቅቱ፡ዐዲስ፡አበባ፡በተመሠረተው፡ባዲሱ፡የአፍሪቃ፡አንድነት፡ድርጅት፡የጤና፡ጥበቃ፡ኮሚቲ፡አማካሪ፡ ኾነው፡ሠርተዋል። በመቀጠል፥ በተባበሩት፡መንግሥታት፡ዓለም፡ ዐቀፍ፡የጤና፡ድርጅት፡ተቀጥረው፡በናይጄሪያ፡በኡጋንዳ፡እና፡ በኮንጎ፡ብራዛቪል፡ባማካሪነት፡ሠርተዋል።

በዚህ፡ሥራቸው፡ላይ፥ በተባይ፡ምክንያት፡በጤናም፡ኾነ፡ በግብርና፡በኩል፡ያለ፟ውን፡ችግር፡የታዘቡት፡አቶ፡ሰይፉ፡ዘለቀ፥ ከተባበሩት፡መንግሥታት፡ጤና፡ድርጅት፡ተሰናብተው፡አገራቸውን፡ በዚህ፡ዘርፍና፡በንግድ፡በኩል፡ለማገልገል፡ተመልሰው፡ኢትዮጵያ፡ ገቡ። በኢትዮጵያ፡የመዠመሪያ፡የተባይ፡ማጥፊያ፡ ድርጅት፡”ኢትዮ፡ፔስት፡ኮንትሮል”ን፡አቋቁመው፥ በንግድ፡ሥራ፡ ላይ፡እያሉ፟፥ የደርግ፡ወታደራዊ፡አገዛዝ፡ሲመሠረት፥ አቶ፡ሰይፉ፡ ወደ፡ስደት፡አመሩ። በመዠመሪያ፡ጅቡቲ፡በነበረው፡የ”ኢትዮ፡ ተባይ፡ማጥፊያ”፡ቅርንጫፍ፡ሲሠሩ፡ቈዩ። እዚያም፡ሳሉ፟፥ ከሌሎች፡ጋራ፡ኾነው፡ርሾ-E.R.S.H.O.፡ “Ethiopian Relief and Self Help Organization”፡የሚባል፡ድርጅትን፡መሥርተው፥ በባቡር፡በግመል፡ከኢትዮጵያ፡ወደ፡ጅቡቲ፡የሚገባው፡ወጣት፡ ስደተኛ፥ ድጋፍን፣ ሕክምናንና፡ወደ፡ውጭ፡አገር፡የሚኼድበትን፡ መንገድ፡የሚሰጥ፡አግልግሎት፡አበረከቱ። ፈረንሳይ፡ከጅቡቲ፡ ስትወጣና፥ በኢትዮጵያም፡በጅቡቲም፡አለመረጋጋት፡ሲስፋፋ፥ አቶ፡ ሰይፉ፡እና፡ባልተቤታቸው፡ወይዘሮ፡አንጄሊና፡ማንጎ፡ወደ፡ ብሪታንያ፡ተሰደዱ። ከዚያም፥ ጡረታ፡እስከሚወጡ፡ድረስ፥ በተላያዩ፡አፍሪቃ-ዐቀፍ፡የቤተ፡ክርስቲያን፡ድርጅቶች፡ባስተዳዳሪነት፡ በኬንያም፡በታንዛንያም፡አገልግለዋል።

አቶ፡ሰይፉ፡ዘለቀ፥ በሕይወታቸው፡ረዥም፡የውጣ፡ውረድ፡ ጕዞ፥ ከ60፡ዓመታት፡በላይ፡ዐብረዋቸው፡ከቈዩት፡ከባልተቤታቸው፡ ወይዘሮ፡አንጄሊና፡ማንጎ፡ጋራ፡ኹለት፡ልጆችን፡አፍርተው፣ አሳድገው፣ አስተምረው፣ የልጅ፡ልጅ፡አይተው፡እስከ፡ መጨረሻው፡በፍቅር፡በደስታ፡እግዚአብሔርን፡እያመሰገኑ፡ኖረዋል። የዘመድ፡አዝማድ፡አባት፣ ለሀገር፡ኵራት፡የታከቱ፡ሰይፈ፡ሚካኤል፡ ዘለቀን፡ነፍሳቸውን፡ይማር፥ በዐጸደ፡ገነት፡ያኑርልን፤ አሜን፨

Happy
Happy
0 %
Sad
Sad
0 %
Excited
Excited
0 %
Sleepy
Sleepy
0 %
Angry
Angry
0 %
Surprise
Surprise
0 %

Average Rating

5 Star
0%
4 Star
0%
3 Star
0%
2 Star
0%
1 Star
0%

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *