የ«ጽምዶ» ቀጠናዊ ወጥመድ፣ የልደቱ አያሌው የታሪክ ግዴለሽነት እና የሕልውና ፖለቲካ ፍልሚያ
ዘ ኢትዮጵያን ትሪቡን
የ«ጽምዶ» ቀጠናዊ ወጥመድ፣ የልደቱ አያሌው የታሪክ ግዴለሽነት እና የሕልውና ፖለቲካ ፍልሚያ
በሥልጣን ሽግግር ስም የርስት ወረራን ሕጋዊ የማድረግ አደገኛ የፖለቲካ ስሌት
በዶክተር ሶስና ታደሰ
(የፖለቲካና ስትራቴጂያዊ ጥናት ክፍል)
የአርታኢ መቅድም
የተቃውሞው ጎራ «የጋራ ጠላትን ለመጣል የሚደረግ ጥምረት ከሁሉም ነገር ይቀድማል» በሚል ሎጂክ እየተመራ ባለበት በአሁኑ ወቅት፣ አንጋፋው ፖለቲከኛ አቶ ልደቱ አያሌው «ጽምዶ እስከምን ድረስ?» በሚል ርዕስ ባቀረቡት መጣጥፍ የወልቃይት፣ ጠገዴ፣ ጠለምትና ራያ የርስት ጥያቄዎችን «ቀይ መስመር» ከማድረግ ተቆጥበን «በስልት (Mechanism)» ላይ ብቻ እንድንስማማ መክረዋል። ይህ ምክር—ከሕወሓትና ከቀጠናዊ ኃይሎች ጋር ስለሚደረገው «ጽምዶ» ጠቀሜታ ከሚናፈሰው ትርክት ጋር ተዳምሮ—በተቃውሞው ጎራ ውስጥ አነጋጋሪ ሆኗል።
ዘ ኢትዮጵያን ትሪቡን ይህንን የዶክተር ሶስና ታደሰ ምላሽ ለአንባቢያኑ የሚያቀርበው፣ በኢትዮጵያና በአፍሪካ ቀንድ ፖለቲካ ውስጥ ያሉ ወሳኝ የሕልውና ጥያቄዎች ግልጽ፣ በማስረጃ የተደገፈና ጠንካራ ክርክር ሊደረግባቸው ይገባል በሚል እምነት ነው። ጸሐፊው የአቶ ልደቱን መከራከሪያ ነጥብ በነጥብ በመሞገት፣ «በስልት እንፍታው» የሚለው አካሄድ በወታደራዊ ኃይልና በስነ-ሕዝብ ምህንድስና የተያዘን መሬት በዲሞክራሲያዊ ሽፋን ሕጋዊ የማድረግ አደጋ እንደሚያዘል ያትታሉ።
ከዚህም ባለፈ ጽሑፉ የ«ጽምዶ»ን ጥምረት እንደ ቀጠናዊ የጂኦፖለቲካ ወጥመድ በመፈረጅ፣ ከዓባይ ግድብ የበላይነት እስከ «ታላቋ ትግራይ» ራዕይ፣ ከግብፅና ከሱዳን የተኪ ጦርነት እስከ ጎንደር ስትራቴጂያዊ መከበብ ድረስ ያሉትን የስጋት ገመዶች ያስተሳስራል።
ትሪቡን በዚህ ጽሑፍ የቀረቡት ትንታኔዎችና መደምደሚያዎች የጸሐፊው መሆናቸውን እየገለጸ፣ ጉዳዩ በተመለከተ የተለያዩ አመለካከቶች ሊደመጡ እንደሚገባ ያምናል። ይህን ምላሽ የምናቀርበውም ውይይቱ በጭፍን ስሜት ሳይሆን በሰከነ ክርክርና በታሪካዊ ማስረጃ እንዲመራ ለማገዝ ነው።
ቅምር
በዶክተር ሶስና ታደሰ የቀረበው ይህ ጽሑፍ፣ አቶ ልደቱ አያሌው «ጽምዶ እስከምን ድረስ?» በሚለው መጣጥፋቸው ያቀረቧቸውን ሁለት ማዕከላዊ ሐሳቦች—ማለትም (፩) ብልፅግናን ለመጣል ከሕወሓትና ከቀጠናዊ ኃይሎች ጋር የሚደረግ «ጽምዶ» አዎንታዊ መሆኑን፣ እና (፪) የወልቃይትና የራያ ጥያቄ «ቀይ መስመር» ሳይሆን «በስልት» ሊፈታ እንደሚገባ—በጥልቀት ይሞግታል። ጸሐፊው መከራከሪያቸውን በአምስት ዋና ዋና ምሰሶዎች ላይ ያቀርባሉ፦
- •«የሽግግር ኦፖርቹኒዝም»፦ ልደቱ የአማራን መዋቅራዊ የሕልውና ትግል ወደ ተራ «የስልጣን ሽግግር» ጥያቄ ዝቅ በማድረግ የትግሉን ማዕከላዊ ግብ ያደበዝዛሉ።
- •የ«ስልት (Mechanism)» ማታለያ፦ «በስልት እንፍታው» ማለት በወታደራዊ ወረራና በስነ-ሕዝብ ምህንድስና የተያዘን ርስት በዲሞክራሲያዊ ሽፋን ሕጋዊ ማድረግ ሲሆን፣ የተጠቂውን ወገን ብቻ እጅ የማስያዝ (Asymmetric Disarmament) አካሄድ ነው።
- •የ«ፕሪቶሪያ» ተረት፦ ሕወሓት «አማራ ላይ አብረን እንዝመት ተብዬ እምቢ አልኩ» የሚለው ትረካ በወታደራዊ ሽንፈት የጠፋን የሞራል የበላይነት ለማስመለስ የተሰራ የስነ-ልቦና ፕሮፓጋንዳ ነው።
- •የ«ጽምዶ» የመጨረሻ ግብ፦ የፈረንሳዩን Africa Intelligence ዘገባ ዋቢ በማድረግ፣ ጥምረቱ የሀገረ-መንግሥቱን መበተን፣ የዓባይን የበላይነት ለግብፅ ማስረከብ፣ «ታላቋን ትግራይ» ማነጽ እና ጎንደርን በስትራቴጂ መክበብ ያለመ ወጥመድ መሆኑን ያሳያሉ።
- •«ተቤዥነት» እና «ድርብ መከላከል»፦ የልደቱ አካሄድ አማራን ወደ ተቤዥነት (Helplessness) የሚከትና ፋኖን ወደ ቀጠናዊ ቅጥረኝነት የሚያወርድ ነው፤ መፍትሔው በ«ብልፅግና»ና በ«ሕወሓት» መካከል መወተፍ ሳይሆን ከሁለቱም ወጥቶ በራስ አቅም መቆም (Double Defense) ነው።
ጸሐፊው በመደምደሚያቸው፣ ሕወሓትን የትግል «አጋር» የማድረግ ማንኛውም ሙከራ «ታሪካዊ ክህደት» መሆኑን አስምረው፣ አማራ አሸናፊ የሚሆነው በራሱ እውነት፣ መርህና ድርጅታዊ ጥንካሬ ላይ ሲመሠረት ብቻ እንደሆነ ይሞግታሉ።
· · ·
ሙሉ ጽሑፍ
መግቢያ፦ የ፴ ዓመታት ዝምታ እና የዛሬው «ፍትሐዊ» መካሪነት ተቃረኖ
አቶ ልደቱ አያሌው «ጽምዶ እስከምን ድረስ?» በሚል ባወጡት መጣጥፍ፣ የብልፅግናን አገዛዝ በፍጥነት ለመጣል በሚል ሽፋን ከሕወሓትና ከቀጠናዊ ኃይሎች ጋር የሚደረገውን «ጽምዶ» (ትብብር) እንደ አወንታዊ የፖለቲካ ክስተት ለማስቆጠርና የርስት ጥያቄዎችን «ቀይ መስመር አታድርጉ፣ በስልት (Mechanism) ብቻ እንስማማ» ብለው ለመምከር ሞክረዋል።
ይሁን እንጂ ላለፉት ፵ ዓመታት የወልቃይት፣ ጠገዴ፣ ጠለምትና ራያ ሕዝብ በሕወሓት የአፓርታይድ ስርዓት ሲጨፈጨፍ፣ ሲፈናቀልና ማንነቱ ሲካድ፤ አቶ ልደቱ አያሌው በሦስት አስርታት የፖለቲካ ዘመናቸው ለአንድም ቀን ድምፅ ሆነዋቸው አያውቁም።
ዛሬ ሕዝቡ በራሱ ደምና መስዋዕትነት ታሪካዊ ርስቱን ካስመለሰ በኋላ፣ አቶ ልደቱ «ወልቃይትና ራያን ቀይ መስመር አታድርጉት፣ ይሄ መመጻደቅ ነው» ብለው ለመሞገት የሚያስችላቸው ታሪካዊ ባለቤትነትም ሆነ ሞራላዊ የበላይነት የላቸውም!
እዚህ ላይ አንድ ሌላ ታሪካዊ ክህደት የፈጸሙበትን አጋጣሚ ማስታወስ እወዳለሁ። አቶ ልደቱ አያሌው፣ ሕወሓት በሁለተኛው ዙር ጦርነት ማለትም ከሰኔ ፳፻፲፫ ጀምሮ ወደ አማራ ክልል ወረራ መክፈቱን ተከትሎ፣ ከቀድሞው የኢሕዴን ሊቀመንበር ታምራት ላይኔ እና ከአቶ ያሬድ ጥበቡ ጋር በመሆን «ለሕወሓት የሰብዓዊ እርዳታ ኮሪደር ይከፈትለት» በሚል የማኀበራዊ ሚዲያ ዘመቻ ከፍተው እንደነበር ይታወሳል።
በወቅቱ በጥላቻ የነደዱ የሕወሓት ታጣቂዎች አቶ ልደቱና ታምራት ላይኔ የተወለዱበትን የላስታ ቀጠና፣ የጁን፣ ጋሸናን በወረራ ይዘው ወደ ጎንደር ጋይንት እየተሻገሩ ነበር። በዚያ አስከፊ የጦርነት ወቅት እነዚያ በጥላቻ የነደዱ የሕወሓት ታጣቂዎች ከቆቦ ጀምሮ፣ ወልድያ፣ ኩል መስክ፣ ላሊበላ፣ ጋሸና፣ ወገል ጤና፣ ደላንታ፣ መቄት ንጹሓንን በጅምላ እየፈጁ፣ የ፹ ዓመት አዛውንት ሳይቀር አስገድዶ መድፈር እየፈጸሙ ነበር።
ይህን ማስታወስ ያስፈለገው ዋና ምክንያት፣ እነ አቶ ልደቱ በወቅቱ ይህን የጦር ወንጀል ከማውገዝ ይልቅ፣ በትግራይ ሕዝብ ስም ለሕወሓት የሰብዓዊ ኮሪደር በሁመራ በኩል ይከፈትለት፣ ከሱዳን የውጭ እርዳታ እህሎች ይግቡ የሚል የሸፍጥ ቅስቀሳ ላይ ስለነበሩ ነው። በወቅቱ በነበረው ሁኔታ የሰብዓዊ እርዳታ ወደ ትግራይ መግባት ያልቻለው ሕወሓት በአማራ እና በአፋር ላይ ወረራ መክፈቱን ተከትሎ እንደሆነ ይታወሳል። እነ ልደቱ ግን የወልቃይት-ጠገዴ፣ ጠለምትና ራያ ብሎም መላው የአማራ ሕዝብ ጉዳይ ግድ ሳይሰጣቸው «በሁመራ በኩል የሰብዓዊ እርዳታ ኮሪደር ይከፈት» የሚለውን የማኀበራዊ ሚዲያ ዘመቻቸው ላይ ተጠምደው ነበር።
ይህ ታሪክ የመዘገበው እውነታ ነው። ይህ ክስተት ራስ-ጠልነት ካልሆነ በስተቀር የሰብዓዊነት መለኪያ ሊባል አይችልም።
እንዲህ አይነት የራስ-ጠልነት ታሪክ ያላቸው አቶ ልደቱ አሁን ደግሞ፣ ለአማራ የነጻነት ታጋዮች የባርነት ካምፕ የሆነውን «ጽምዶ» ዓላማው እንዲሳካ፣ የፋኖ ኃይሎች የርስት ጥያቄዎችን «ቀይ መስመር አታድርጉ፣ በስልት (Mechanism) ብቻ እንስማማ» ብለው ለመምከር ሞክረዋል።
ይህ አቀራረብ የአቶ ልደቱን ነባር የርስትና የማንነት ግዴለሽነት የሚያንፀባርቅ፣ የሕወሓትን መዋቅራዊ የጥፋት አቅም የሚያለሰልስ እና የአማራን ሕዝብ የሕልውና ትግል ወደ ሌላ የባርነት ካምፕ ለመንዳት የታለመ «የፖለቲካ አቋራጭ» (Political Shortcut) ነው።
፩. «ትራንዚሽናል ኦፖርቹኒዝም» (Transitional Opportunism)፦ የልደቱ አያሌው አዲስ የፖለቲካ ካርታ
የአቶ ልደቱ መከራከሪያ መሰረታዊ ስህተት የሚጀምረው ከፖለቲካዊ ግቡ አወቃቀር ነው። ልደቱ የኢትዮጵያን ችግር «የሥልጣን ላይ አገዛዝን የመቀየር» (Regime Change) አጀንዳ አድርገው ብቻ ያዩታል። ለአቶ ልደቱ አገዛዙ ከተወገደና «ሁሉን አቀፍ የሽግግር መንግስት» ከተቋቋመ የፖለቲካው ስራ ተጠናቋል።
ነገር ግን የአማራ ሕዝብ እየታገለው ያለው በቀላሉ የሥልጣን ተዋናዮችን ለመቀየር ሳይሆን፣ ላለፉት ፴፭ ዓመታት የተጫነበትን መዋቅራዊ የሕልውና አደጋ፣ የዘር ማጥፋትና የታሪካዊ ርስት ወረራ ለመቀልበስ ነው። ይህ ትግል አገዛዝን ለመጣል ብቻ የሚደረግ ሳይሆን ሥርዓትን ለመቀየር የሚደረግ ትግል ነው። የአማራን ሕዝብ ለሕልውና አደጋ ያጋለጠው ሥርዓት መዋቅራዊ ቅርጽ የያዘው ድኀረ-፲፱፻፹፫ በመሆኑ፣ ባለፉት ፴፭ ዓመታት የሕልውናው አደጋ የሆነውን፣ የአገር ባለቤትነቱን የነጠቀውን ሥርዓት ለመገርሰስ የሚደረግ ትግል ነው።
የአቶ ልደቱ ትረካ የሕልውና ጥያቄን ወደ ተራ «የስልጣን ሽግግር ፖለቲካ» (Transitional Politics) ዝቅ በማድረግ የትግሉን ማዕከላዊ አላማ ያደናግራል። ይህ እውነታ ዕድሜ ዘመናቸውን ከመላው አማራ ሕዝብ ድርጅት (መአሕድ) ጀምሮ ላለፉት ፴ ዓመታት በፖለቲካው ዓለም ከቆዩት አቶ ልደቱ አያሌው የተሰወረ ባይሆንም፣ ከ፲፱፻፷፮ ጀምሮ በአማራ ደም የሌሎች ሥልጣን ይቀደም የሚለውን ሀሳብ የሚጋሩ በመሆናቸው የፈጠሩት የትግል ትርክት ማዛባት እንደሆነ እንረዳዋለን።
፪. የ«Mechanism» (ስልት) ማታለያ፦ የርስት ወረራን በዲሞክራሲያዊ ሽፋን የማፅደቅ ሴራ
አቶ ልደቱ በጽሑፋቸው፦ «በወልቃይትና ራያ ጉዳይ አማራ ወይም ትግራይ ይሁን በሚለው መፍትሔ ላይ አሁን መስማማት የለብንም፤ ይልቁንም በምን ስልት (Mechanism) እንዲፈታ መስማማት አለብን» ይላሉ። «ቀይ መስመር» የሚሉ አካላትንም «ይመጻደቃሉ» በማለት ይነቅፋሉ።
ይህ መከራከሪያ መዋቅራዊ የሆነ አደገኛ የፖለቲካ ወጥመድ አቅፎ ይዟል፦
- •የ«Mechanism» አፓርታይድ፦ ሕወሓት በ፲፱፻፹ዎቹ በወታደራዊ ኃይል የወሰዳቸውን የወልቃይት፣ ጠገዴ፣ ጠለምትና ራያ መሬቶች ላይ የትግራይ ሰፋሪዎችን በማስገባት የስነ-ሕዝብ ምህንድስና (Demographic) ለውጥ አድርጓል። አሁን ላይ ቆሞ «በሕዝበ-ውሳኔ ወይም በሕገ-መንግስት ማሻሻያ እንፍታው» የሚል ስልት መቀበል ማለት፦ በወታደራዊ ወረራና በዘር ማጽዳት የተያዘን መሬት በዲሞክራሲያዊ ሽፋን ሕጋዊ (Legitimize) ማድረግ ነው!
- •የእጅ ማስያዝ አጣብቂኝ፦ ሕወሓት ዛሬም ድረስ «ወልቃይትና ራያ የትግራይ ግዛቶች ናቸው፤ አንዲት ስንዝር አትቆረስም» እያለ በሚፎክርበት ሰዓት፣ የአማራን ሕዝብ ብቻ «ቀይ መስመር አታብዛ፣ በስልት ተስማማ» ማለት—የተወረረውንና የተጠቃውን ወገን ብቻ እጅ ማስያዝ (Asymmetric Disarmament) ነው።
ሞጋች ጥያቄ ፩
«በኃይልና በወረራ ተወስዶ ከፍተኛ የዘር ጭፍጨፋ የተፈጸመበትንና የስነ-ሕዝብ ስብጥሩ በወረራ የተቀየረን ርስት ‹በሕዝበ-ውሳኔ ወይም በሕገ-መንግስታዊ ስልት (Mechanism) እንፍታው› የሚል ውል መቀበል፤ ቀድሞ የተፈጸመን የዘር ማጽዳትና የወታደራዊ ወረራ ውጤት በዲሞክራሲያዊ ሽፋን ማፅደቅ አይደለምን?»
፫. «የፕሪቶሪያው ስምምነት» ተረት እና የሕወሓት የፖለቲካ ማደንዘዣ
ሕወሓት «በፕሪቶሪያ ወቅት ብልፅግና በአማራ ላይ አብረን እንዝመት ብሎ ጠይቆን እምቢ አልን» በሚል የሚያራግበው ትረካ፣ በወታደራዊ ተሸናፊነቱ ያጣውን የሞራል የበላይነት ለማስመለስ የተሰራ የሥነ-ልቦና ፕሮፓጋንዳ (Psychological Warfare) ነው።
በፕሪቶሪያ ስምምነት ወቅት (ጥቅምት ፳፻፲፭ ዓ.ም) ሕወሓት በከባድ ወታደራዊ ከበባና ውድቀት ውስጥ ነበረ። ከመቀሌ ውጭ ሁሉም የትግራይ ትልልቅ ከተሞች ተይዘውበት ነበር። መቀሌ በሰዓታት ውጊያ የመያዝ ዕድል እያለ፣ ሕወሓት የፈረመው «የፕሪቶሪያው ስምምነት» ለሕልውናው ሲል ተንበርክኮ እጁን የሰጠበት እንጂ፣ አቻ ሆኖ በጉልበቱ የፈጠረው ዕድል አልነበረም። በመቀጠል ኬንያ ላይ የተደረገው የከፋው አፍራሽ ስምምነትም አሁንም አማራን ለመጉዳት ያለመ እንጂ ከማዕከላዊ መንግሥት «አብረን እንዝመት» የሚል ድርድር ቀርቦለት እምቢ ያለበት አይደለም። እንዲያም ሆኖ፣ ሕወሓት ይህንን የሐሰት ትረካ በመንዛት የትግራይን ሕዝብ ለማጽናናትና የአማራን ትግል (ፋኖን) በስነ-ልቦና ለማደንዘዝ ሲሞክር፤ አቶ ልደቱ ደግሞ «የርስት ጥያቄን በ Mechanism እንፍታ» በሚል የፖለቲካ አቋራጭ ለዚሁ የሕወሓት ሴራ የንድፈ-ሐሳብ ከለላ ይሰጣሉ።
፬. የአፍሪካ ኢንተለጀንስ (Africa Intelligence) ዘገባ እና የ«ጽምዶ» የመጨረሻ ግብ
በወታደራዊ እና በደህንነት ጉዳዮች ላይ በልዩ ትኩረት የምርመራ ዘገባዎችን የሚያቀርበው የፈረንሳዩ Africa Intelligence መጽሔት ባወጣው አዲስ መረጃ፣ በካርቱም፣ ፖርት ሱዳን እና በትግራይ (አክሱም) ሚስጥራዊ ቦታዎች የተካሄደው «ጽምዶ» የተባለው ስብስብ ውስጣዊ ተቃረኖውና አደገኛ ቀጠናዊ ባህሪው ይፋ ሆኗል።
Africa Intelligence — “Distrust clouds Tsimdo, the growing anti-Abiy front” (01/06/2026)
ዘገባው ይፋ እንዳደረገው፦ «የጎጃም ክንፍ ከሕወሓት ጋር ለሚደረግ ጥምረት ይበልጥ ፈቃደኝነት ሲያሳይ፤ በአንፃሩ ለተከራካሪው የወልቃይት አቅራቢያ የሚገኘው የጎንደር ፋኖ ክንፍ ግን ይህንን ጥምረት በጽኑ ይቃወማል።» ይላል።
ልደቱ «ወልቃይትና ራያን ቀይ መስመር አታድርጉት፣ ይሄ መመጻደቅ ነው» የሚሉት የጎንደሩን የፋኖ ክንፍ ይመስላል። በርስቱ ጉዳይ ታሪካዊ ባለቤትነትና ሞራላዊ የበላይነት ያለውን የፋኖ ኃይል ከመሰረታዊ የትግል ዓላማው መስመሩን ለማሳት፣ አበይት የሆነውን ጥያቄ (Grand Cause) ወደ ንዑስ ጥያቄ የማውረድ ዓላማ ያለው አቀራረብ ነው።
ይህ ሁኔታ፣ በ፳፻፲፯ ዓ.ም በወቅቱ በነበረው አደረጃጀት የአማራ ፋኖ ብሔራዊ ኃይል የጎጃም ቀጠናዊ ትስስር ኃላፊ የነበረው ፋኖ የቆዬ ሞላ ከሕወሓት ጋር አብሮ ለመስራት ለማሳመን ከተጠቀመው ምሳሌ ጋር ይመሳሰላል። የፋኖ አመራሩ «የነ ወልቃይትን ጉዳይ አራት ኪሎ ከገባን በኋላ ሻይ ቡና እያልን በጋራ እንወስናለን» ነበር ያለው። እንዲህ ያለው ታሪካዊ የክህደት ንግግር በአቶ ልደቱ ጽሑፍ ላይ በምሁራዊ ሸፍጥ መልኩ ቀርቧል።
ጸሐፊው ወደ ጎን ገፍትረው ያለፉትና በ«ጽምዶ» ስም ሊተገበር የታሰበው የመጨረሻውና የታለመው ግብ (Ultimate Master Plan) ምንድነው?
- የሀገረ-መንግሥቱን አከርካሪ መስበር፦ ኢትዮጵያን በደካማ የኮንፌዴሬሽን መዋቅር መበተን፤
- የዓባይንና የሕዳሴውን ግድብ የበላይነት በተኪ ጦርነት (Proxy War) ለግብፅ ማስረከብ፦ በ፲፱፻፹፫ቱ የ«ፈለገ ግዮን» ሰነድ መሠረት መተከልን ማዳከም/መነጠል እና የተከዜ ተፋሰስን በሕወሓትና በሱዳን አል-ቡርሃን ቁጥጥር ሥር ማድረግ፤
- የ«ታላቋ ትግራይ» ሕልምን እውን ማድረግ፦ ሕወሓት የወልቃይት-ሁመራን «የአማራውን የሆርሙዝ ቁልፍ» በመቆጣጠር፣ እስከ መተማና ቤኒሻንጉል ድንበር በመዘርጋት ትግራይን በ«ሶማሌላንድ ሞዴል» የመገንጠል አላማውን ማሳካት፤
- የጎንደርና የአማራ ሕዝብ መከበብ (Strategic Encirclement)፦ ትግራይ እስከ መተከል፣ በደቡብ ደግሞ የ«ግዮን/ኮንፌዴሬሽን» ፍላጎት ያላቸው አመራሮች እስከ መተከል ሲመጡ፤ ሁለቱ አካላት በመተከል መስመር የቀጥታ ድንበር ይፈጥራሉ።
በዚህም ጎንደር የታሪካዊ ርስቶቿና የውጭ መውጫ ኮሪደሮቿ ተነጥቀው፦ ያለምንም የመተንፈሻ ኮሪደር በመሃል በጠላት የተከበበች ደሴት (Encircled Enclave) እንድትሆን ለማድረግ የታቀደው የጂኦፖለቲክስ ሸፍጥ ነው።
ሞጋች ጥያቄ ፪
«ዓለም አቀፍ የደህንነት ዘገባዎች እንኳ ‹ጽምዶ› በግብፅና በሱዳን የተኪ ጦርነት ተደግፎ የወልቃይትንና የመተከልን ኮሪደሮች ለመክበብ የታለመ ሴራ መሆኑን እያረጋገጡ ባሉበት ሰዓት፤ አቶ ልደቱ ይህንን የከሰረ ጥምረት ‹የፖለቲካ ብስለት› አድርገው ሊሸጡልን የሚሞክሩት በምን ስሌት ነው?»
፭. የ«ተቤዥነት» (Helplessness) ስነ-ልቦና እና የ«ድርብ መከላከል» (Double Defense) ፅናት
አቶ ልደቱ «ብልፅግና ያጋረጠው አደጋ ከፍተኛ ስለሆነ ከማንም ጋር—እንኳንስ ከሕወሓት ጋር ይቅርና ከታሪካዊ ጠላቶች ጋር እንኳ መተባበር ይገባል» ሲሉ ይከራከራሉ።
ይህ አቀራረብ የሚከተሉትን ስትራቴጂያዊ አደጋዎች ይፈጥራል፦
- •የሥነ-ልቦና ስብራት፦ የአማራን ሕዝብ የሕልውና ትግል «በራሱ አቅምና መርህ መቆም አይችልም» የሚል ተቤዥነት (Helplessness) ውስጥ በመክተት፣ ሁልጊዜም ቢሆን ከሌላ አዳኝ ኃይል ጋር መጣመር እንዳለበት አድርጎ ያስባል።
- •ከነፃነት ታጋይነት ወደ ተራ ቅጥረኛነት፦ ብልፅግናን ለመጣል ሲባል ከሕወሓት ጋር መጠመድ፣ የአማራን የትጥቅ ትግል ለቀጠናዊ ቁማርተኞች መጠቀሚያ በማድረግ ፋኖን ወደ «ዳግማዊ ኢሕዴን» ደረጃ ዝቅ ያደርገዋል። ከዚያም ሲከፋ ፋኖን በሕወሓቱ «አርሚ ፸» ሞዴል የቀጠናው ቅጥረኛ ተዋጊ የማድረግ፣ ከሕልውና ታጋይነት አውጥቶ ወደ local agent ማውረድ ነው።
- •የመጥፋት አዙሪት፦ አንድን አምባገነን (ብልፅግናን) ለመጣል ሲባል፣ ሌላኛውን ሥርዓታዊና መዋቅራዊ ጠላት (ሕወሓትንና ኦነግን) ማጠናከር ከተቃጠለ ቤት ወጥቶ ወደ ተናዳፊ እባብ ጉድጓድ የመግባት ያህል አደገኛ ነው።
በጅቡና በእባቡ (በብልፅግናና በሕወሓት) መካከል የቆመ አካል ሊያደርግ የሚገባው «ከሁለቱ አንዱን የመምረጥ ግዴታ ውስጥ መውደቅ አይደለም፤ ከሁለቱ ከመሃላቸው መውጣት ነው!»
ከመሃል መውጣት ማለት ከትግል መሸሽ ሳይሆን፣ የሌሎችን የፖለቲካ አጀንዳ ከመሸከም ወጥቶ በራስ መርህ፣ በራስ አቅም እና በራስ ድርጅታዊ ጥንካሬ ላይ ቆሞ ሁለቱንም አደጋዎች እኩል የመመከት (Double Defense) ፅናት ማሳየት ነው።
መደምደሚያ
አቶ ልደቱ አያሌው ያቀረቡት «ጽምዶ እስከምን ድረስ?» የሚለው ጽሑፍ፣ የብልፅግናን አገዛዝ በፍጥነት ለመጣል በሚል ስም የወልቃይት-ጠገዴ፣ ጠለምትና ራያን ደም ዋጋ ወደ ጎን ገፍትሮ «በሂደት በ Mechanism እንነጋገርበታለን» የሚል ማደንዘዣ የሚያቀርብ ፖለቲካዊ አቋራጭ (Political Shortcut) ነው።
የአማራ ሕዝብ ባለፈው ግማሽ ክፍለ ዘመን የደረሰበትን መከራ የተረዱ፣ ይህን መዋቅራዊ የጥቃት መሰረት ከጥፋት ጥንስሱ (ሕወሓት) እስከ ውርስ አስቀጣዩ (ኦሕዴድ-ብልፅግና) ድረስ ያሉ ጠላቶችን ጠንቅቀው የተረዱ እውነተኛ ፋኖዎችና መሬት ላይ ያሉ የሕዝብ መዋቅሮች የ«ጽምዶ»ን ወጥመድ ውድቅ በማድረግ፣ የአማራ አላማ ያለውና በጥብቅ ዲሲፕሊን የሚገዛ አታጋይ ድርጅት በመፍጠር አማራ ሕልውናውን በክንዱ ያስከብራል። አማራን ማጥፋት የፖለቲካ እስትንፋሱና የሕልውናው መሠረት ያደረገውን ሕወሓት የትግል ‹አጋር› ለማድረግ የሚደረጉ የትኛውም ጥረቶች ታሪካዊ ክህደት ተብለው ይመዘገባሉ።
የአዋቂ አጥፊዎቹን አቶ ልደቱን ጨምሮ ነገ በታሪክ ፊት ለሚጠየቁ ሁሉ ማስታወስ የምንፈልገው እውነታ፡- ሕወሓት ትናንትናም ሆነ ዛሬ ጦር የሚሰብቀውና የሰበቀው አማራን ለማጥፋትና አጽመ-ርስቱ የሆኑትን ወልቃይት-ጠገዴ፣ ጠለምት፣ ራያና ኮረምን ለመውረር እንዲሁም ታላቋን ትግራይ ለመመስረት ብቻ ነው። የዚህ የጥፋት ኃይል አጋር ሆኖ መሰለፍ ጸረ-አማራነት ነው።
የአማራ ሕዝብ በአሁኑ ወቅት እየታገለው ያለው ለፍትሕ፣ ለሕልውናው መረጋገጥ፣ ለታሪካዊ ርስቶቹ መከበርና የሀገር ባለቤትነቱን በዘላቂነት ለማረጋገጥ እንጂ የሌሎች ስልጣን ፈላጊዎች ወይም የቀጠናዊ ኃይሎች መጠቀሚያ ለመሆን አይደለም።
በጥቅሉ የአማራ ሕዝብ አሸናፊ የሚሆነው አንዱን በዳይ በሌላ በዳይ ለመተካት ሲሮጥ ሳይሆን፤ በራሱ የእውነትና የፍትሕ ጥያቄ፣ በራሱ አማራዊ መርህ እና በራሱ በተስተካከለ ድርጅታዊ ጥንካሬ ላይ ጸንቶ የራሱን አሸናፊ መስመር ሲጠርግ ብቻ ነው!!
ድል ለእውነተኛ አርበኞች
ድል ለአማራ ሕዝብ!!
